ከፋሺስት ኢጣሊያ ድል መሆንን ተከትሎ የትምህርት ቤቶች መከፈት

ይህ ወቅት ሃገሪቷ ገና ወደ መረጋጋቱ ሙሉ በሙሉ ያልገባችበት ነበር፡፡በወቅቱ ስለነበረው ሁናቴ ብርሃንና ሠላም ጋዜጣ ሐምሌ ፲፮ ቀን ፲፱፻፴፱ ዓ.ም ባወጣው ጽሑፍበኢጣሊያ አጥቂነትና ግላዊነት አምስት ዓመት በሆነው ግፍ የኢትዮጵያ አገሮች ጠፉ ኢጣሊያ ያጠፋችው አገሩን ብቻ አይደለም የሰውን ልብ በጠበጠችው መንፈሱንም ገልብጣ የኢትዮጵያዊው አሳብ ተሽሮ ኢጣሊያዊ አሳብ እንዲተካ ጣረች በዚህ መካከል ይኖር የነበረው ሕዝብ ትክክለኛ ኑሮው ተናጋ የኑሮውም መሠረት አሳቡ ሁሉ ተናወጠ ሲል ይገልጸዋል፡፡

ብርሃኑ ድንቄም ቄሳርና አብዮት በሚለው መጽሓፋቸው ከኢጣሊያኖች ይዞታ በኋላ የኢትዮጲያ ህዝብ አሰተሳሰብ በፍጹም እንደተለወጠ ያልተገነዘበ አይገኝም ግን አለዋወጡ በግልጥ ፎርም እና አንጻር አልነበረውም …በዚያን ጊዜ ያለ ጥርጥር የአገር ፍቅር ስሜት በጣም ጠንካራ ነበር፡፡ ነጻነትን አጥቶ የባዕድ ተገዥ መሆን ትልቅ ትምህርት ሆኖታል ሲሉ ገልጸውታል፡፡

በእንግሊዞች እርዳታና በአርበኞች ጽኑ ትግል የአምሥቱ የመከራ ዓመታት በሚያዚያ @7 ቀን ፲፱፻፴፫ ዓ.ም ኢትዮጵያ በእግዚአብሔር ቸርነት እንደተፈጸመ ለማገገም ስትል ወዲያውኑ ግንቦት ፪ ቀን ፲፱፻፴፫ ሚኒሰትሮቿን ሾመች፡፡ ሁለተኛው የትምህርት ቤቱ መከፈት ታሪክ የሚጀምረው ከ፲፱፻፴፬ ጀምሮ ነው በተለይ እሰክ ፲፱፻፶፯ ያለውን ለሚያካትተው የትምህርት ቤቱ ታሪክ ቀደም ሲል የሁለተኛው የዓለም ጦርነት ሙሉ በሙሉ ባለመጠናቀቁ የትምህርት መሣሪያዎችና መፃሕፍት ግብዓቶች ከአውሮፖ የሚመጡ ስለነበሩ ከፍተኛ ችግር ውሥጥ ነበር::

ይህንኑ ችግር ለመፍታት እሰከ ፲፱፻፴፰ ዓ.ም መጠበቅ ግድ ነበር ፡፡ በ፲፱፻፴፰ ዓ.ም ዶክተር ማት የተፈሪ መኰንን ት/ቤት ዳሬክተር ሲሆኑ አስፈላጊ የትምህርት መሣሪያዎችን ከአሜሪካንና ከእንግሊዘ አገሮች ገዝተው እንዲያመጡ ተላኩ፡፡ ይኽም ወቅት ፪ኛው የዓለም ጦርነት ፍጻሜ አግኝቶ ስለነበር የሳይንስ መሣሪያዎች/ኘሮጀክተር/ ፊልም የሚታይባቸው ዕቃዎች/ላንቴርን ስላይድ/ የፊልም ጥቅሎች በትምህርት ቤት አስፈላጊ የነበሩ መማሪያዎችን ለማግኘት ተቻለ (ያልታተመ ጥናታዊ ጽሁፍ ገፅ ፲፱)፡፡

በ፲፱፻፴፱ና በ፲፱፻፵ ት/ቤቱ በጣም የተሰፋፉበት ዘመን ነበር፡፡ በ፲፱፻፴፱ የተማሪዎች ብዛት ፲፪፻፲ ሲሆን በሙሉ ወንዶች ነበሩ (ያልታተመ ጥናታዊ ጽሑፍ ሠንጠረሽ ፫/ሀ/) ፡፲፱፻፴፮-፷፫ የት/ቤቱ እንቅስቃሴ ይካሄድ የነበረው በካናዳውያን/Jesuits ወይንም ኢየሱሳዊያን የካቶሊክ መምህራን ነበር፡፡ የትምህርት አሰጣጡንም ሆነ የተማሪዎቹዲስፕሊን በካናዳውያኑ ይሠራ ስለነበር የአሠራሩ ባህርይ በውጭ ዜጐች ሙሉ ቁጥጥር ሥር ነበር፡፡የአማርኛ ቋንቋን ሳይቀር የሚያስተምሩት ካቶሊካውያኑእንደነበሩ በወቅቱ የነበረውን ሁኔታ ደጃዝማች ወልደሰማዕት ገብረወልድ ተናግረዋል፡፡

Scroll to Top